Tuesday, June 8, 2010

የአስተዳደር ቦርዱ የአባላትን መብት ከመርገጥ አልፎ ጨፈለቀው !

እዚህ ይጫኑበአስተዳደር ቦርድ ችሎታ ማነስ ምክንያት እየደረሰ ያለውን ከፍተኛ ጥፋት በወቅቱ ለማስቆምና የሚበጀውን ሰላም ለማምጣት ሲሉ ግለሰቦች ፤ሽማግሌዎችና የሰላም ልዑካን ሁሉ ብዙ ጥረት ቢያደርጉም ድካሙ በአስተዳደር ቦርዱ እምተኝነት ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ይሁን እንጂ ጥረቱን በመቀጠልና ተስፋ ባለመቁረጥ የቤተክርስቲያኑ የወደፊት ሁኔታና ዕጣ እጅግ አድርጎ ያሳሰባቸው ቁጥራቸው ከ35 በላይ የሚሆኑ የቤተክርስቲያኒቱ አባላት ለተፈጠረው ችግር መፍትሔ ለመሻትና ሌሎች ጉዳዩ ይመለከተናል የሚሉትን አባላት ሁሉ ጨምረው ለመወያየትና በጋራ መፍትሔ ለመፈለግ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ጥያቄ በጽሑፍ ቢያቀርቡም የአስተዳደር ቦርዱ በተለመደው የእንቢተኝነት ባሕርዪው አዳራሹን መጠቀም እንደማይችሉ በመግለጽ ከልክሏል፡፡ 

በምትኩም ስማቸውንና ፊርማቸውን በወረቁቱ ላይ አስፍረው ጥያቄ ያቀረቡትን ግለሰቦችና ስብሰባው እንዲካሄድ ሕዝቡን በቀና ልብ በማስተባበር ለቦርድ ያቀረቡትን ግለሰብ ስም በማጥፋትና የኢትዮጵያ መንግሥት ደጋፊና የመጀመሪያዋ እመቤት የቅርብ ዘመድ ናቸው በማለት የሰንበቴ ተለዋጭ በሆነው አዲስ የቦርድ ብሎግ አማካኝነት እያጥላላ ይገኛል፡፡

የሕዝብን ድጋፍ ባላገኘውና በቦርድ ብቸኛ ሥልጣን ያለ አግባባ ጸድቋል በተባለው ባይሎው መሠረት ከመቶ አሥር ፐርሰንቱ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ስብሰባ እንዲጠራላቸው ቢፈልጉ ይችላሉ የሚለውን ሕግና ለአባላት የቆመውን መብት በመጋፋት ቦርዱ የአባላቱን መብት ከመርገጥ አልፎ በኃይል ጨፍልቆታል፡፡

የሰው ልጆች መብት ከምንም በላይ በሚከበርበት በአሜሪካን ሃገር ተቀምጦ የሰውን ያውም የክርስቲያኖችን መብት መርገጥ የቤተክርሰቲያኒቱን ሕግ አለማክበር ብቻ ሳይሆን የአሜሪካንን ብሔራዊ ሕገ መንግሥት መናቅና አለመቀበልም ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከፍተኛ ወንጀል ነው፡፡

አንድ የቤተክርስቲያን አባል በቤተክርስቲያኑ መተዳደሪያ ሕግ የተቀመጠለትን ሕግ አክብሮ መሄድና ማድረግ የሚገባውን ነገር ሁሉ ሕግን ተከትሎ ማድረግ ካልቻለ የእርሱ መብት መከበር ምኑ ላይ ነው ? ሠላሳ ብሩን እየከፈለና ግዴታውን እየተወጣ መብቱ የቦርድ እንጂ የአንተ አይደለም ከተባለ የአባልነት ትርጉሙስ ምንድን ነው ? ትናንት አባላት አይደላችሁምና በዚህ ቤተ ክርስቲያን ምንም አያገባችሁም ተብለው ወደ ጎን ከተገፈተሩት መሥራች የቤተክርስቲያኑ አባላትስ በምን መለየት ይቻላል ? እነርሱም እኮ ፍርድ ቤት የቆሙት በሌላ በምንም ምክንያት ሳይሆን የአባልነት መብታችን ተረገጠ፡፡ ቦርድ አምባገነን ሆኖ እንደባሪያ ልግዛችሁ አለን፡፡ በቤተ ክርስቲያን እኩል መብት እንዳለን ይረጋገጥልን በሚል እኮ ነው፡፡ 

በሌላም በኩል አንዳንድ ሰዎች ባለማወቅ የቤተ ክርስቲያንን ነገር እንዴት በሆቴል ውስጥ ተሰብስበው ይነጋገራሉ በማለት ተሰብሳቢዎችን ሲተቹ ይሰማሉ ፡፡ ነገር ግን ሁኔታውን ሚዛናዊ አድርገን ስናየው አባባሉ ትክክል ሆኖ አናገኘውም፡፡ ዜሬ አኮ በቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ ከሚደረገው የአባላት ስብሰባ ይልቅ በሆቴል ቤት ውስጥ የሚደረጉት ስብሰባዎች የተሻለ የስብሰባ ሥርዓት እየታየባቸው መጥቷል፡፡ ቦርድና መሰሎቹ ቤተክርስቲያኗን የሥርዓት አልበኞች መዲና አድርገዋታል፡፡ቦርድን ለመደገፍና ሺ ዓመት ያንግሥህ ለማለት ካልሆነ በስተቀር የቦርድን ሥህተት ለማረም የሚጠራ ስብሰባ ተፈላጊ አልሆነም፡፡ ክርስቲያኖች ስለ ቤተ ክርስቲያናቸው ችግርና ስለ መፍትሔው በገዛ ቤተ ክርሰቲያናቸው ውስጥ መሰብሰብና መወያየት ካልቻሉ ታዲያ የት ይወያዩ ? ስድስትና ሰባት የቦርድ አባላት ይህንን ሁሉ ሕዝብ አሻንጉሊት አድርገው እንዴት ይጫወቱበታል ?

ስለዚህ ቦርዱ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እያደረሰ ያለውን ከፍተኛ አደጋ ዝም ብለው እያዩና ከንፍርን ብቻ እየመጠጡ ከመቀመጥ ይልቅ በሆቴልም ይሁን በየትም አመቺ በሆነ ቦታ ተሰባስቦ በመወያየት ለችግሩ መፍትሔን መፈለግ ጊዜ የማይሠጠው ጉዳይ ነው በማለት ሰላም ተዋሕዶ አስተያየቷን ትቸራለች፡፡

አለበለዚያ ግን ‹ በፊት ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ ፤ አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ፡፡› የሚለው ተረት በሁሉም ላይ ደርሶ መያዣ መጨበጫ ከማጣት በፊት የአስተዳደሩን አካሄድና የወደፊት አኩይ ዓላማ ቀድመው ከተረዱ ወገኖች ጋር አብሮ በመሆን ችግሩ የሚወገድበትንና ቤተ ክርስቲያኒቱ ሰላም የምታገኝበትን መንገድ መፈለጉ አማራጭ የሌለው መፍትሔ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጠይቀውን ግዴታ ሳይወጡ ዳር ሆኖ ማየት ግን በራሱ መፍትሔ አይደለምና የድርሻችንን እንወጣ፡፡

1 comment:

  1. ሰላም ለሁላችሁ ይሁን

    ሰሞኑን ወደ ዳላስ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ከስራ በተባረሩት በመላከ አርያም አወቀ ምትክ አንድ መነኩሴ ተደራድረው ተቀጥረዋል ይባላል እውነት ነው ?

    ReplyDelete

አስተያየት