Friday, November 26, 2010

ክራባት ! የሰላዩ ብዕር 
ረዳት ካሜራ
ክፍል ሦስት
እኔም በበኩሌ የባለቤቴ ጠባይ ባልተጠበቀ ሁኔታ መለወጥና በትዳራችን መካከል የነበረው ጣዕም ያለው ፍቅር እየቀዘቀዘ መምጣት እጅግ በጣም አሳስቦኝ ነበር ፡፡ እስከ ሕይወቴ ፍጻሜ ድረስ ከእርሷ ጋር ለመኖር ወስኜና ወድጃት ያገባኋት የትዳር ጓደኛዬን ከምንም በላይ እወዳታለሁ፡፡እርሷ ስሜታዊ ሆና በየምክንያቱ ብትበሳጭም ብስጭቷን የሚያበርድ እንጂ ንዴቷን የሚጨምር ሥራ ሠራሁ የምለው በእኔ በኩል አንዳች ነገር የለም፡፡እሷን የሚያስቀይም መጭፎ ነገር ማደረጌም ጨርሶ ትዝ አይለኝም፡፡ ይሁን እንጂ ለምታሳየኝ አክብሮት ለሌለው ሥነ ምግባሯ ቂም ይዤ ወይም እርሷን በክፉ ለመበቀል በጭራሽ አልሜም አስቤ አላውቅም፡፡የእኔ የሁሉ ጊዜ ምኞት እርሷ በአእምሮዋ ታድሳና ተለውጣ ማየት ነው፡፡ ወዲያው መልሳ ብትረሳውም ከእርሷ ያየሁትና የምወድላት መልካም ነገር ቢኖር ካጠፋች በኋላ የምታደርገው ጸጸት ነው፡፡ ያ እንዳልሰለቻትና እንዳልጠላት አድርጎኛል፡፡
ሰላዩ ብዕር ! ክፍል ሁለት
ከባለቤቴ ጋር ከተጋባን አምስት ዓመታት አለፉን ፡፡ በሰላምና በጥሩ ፍቅር አሳለፍን የምላቸው ዓመታት ቢኖሩ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ዓመታት ብቻ ናቸው፡፡ በእነዚህ ዓመታት ውስጥ በመካከላችን በሚፈጠሩ ችግሮች ዙሪያ መነጋገሩ ፤ መወያየቱና መግባባቱ ነበረን፡፡ ከሁለት አንዳችን ቅሬታ የተሰማው ሰው ካለ በግልጽ ‹ በዚህ ጉዳይ ቅር ስላለኝ መነጋገር እፈልጋለሁ › ካለ ሁለታችንም ያለምንም ተቃውሞ ለመነጋገር በደስታ እንቀመጣለን፡፡ መግባባት ባለበት ሥርዓት እንነጋገራለን ፤ እንደማመጣለን፡፡ይህ ባህሪያችን በመካከላችን ያለውን መተማመንና ፍቅር ጥሩ ደረጃ ላይ አድርሶት ነበር፡፡ 

Wednesday, November 10, 2010

       
ሰላዩ ብዕር
በዚህ ዓለም የምናየው ከፍተኛውና አስገራሚው የቴክኖሎጂ ውጤት ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድና ስጦታ ነው፡፡ እግዚአብሔር የሰው ልጅን ሲፈጥረው በመልካም ሁኔታና በምቾት እርሱን እያመሰገነው እንዲኖር ነበር፡፡ ለዚህም አዳምን ከመፍጠሩ በፊት ቀድመው ለሰው ልጅ የምቾት ኑሮ የሚያስፈልጉ ነገሮች ሁሉ መፈጠራቸው ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ሰው እንዳይራብና እንዳይጠማ አስቀድሞ ምግብንና መጠጥን እግዚአብሔር ፈጥሮ አዘጋጀለት፡፡ እንዲሁም የሰው ልጅ በተስተካከለ የአየር ንብረት እንዲኖር ሁኔታዎች ሁሉ ተመቻቹለት፡፡ይህም እግዚአብሔር ሰውን ደስ እያለው እንዲሮር መፍጠሩን ያስገነዝበናል፡፡ ነገር ግን ስው ከተፈቀደለት የኑሮ አጥር ዘሎ ባልተፈቀደለት የሕግ ማፍረስ ኑሮ ውስጥ ሲገባ ፤ ሁኔታዎች ሁሉ ተለዋውጠው ተገላቢጦሽ ሆኑበት ፡፡ በፈጸመው ስህተት የሰው ልጅ ተፈጥሮን በራሱ ጥረትና ወዝ እየታገለና እያቀና እንዲኖር በፈጣሪ ተወሰነበት ፡፡